Monday, July 30, 2012

ትዝ ይለኛል



ትዝታ በየሁሉም ሰው ልብና ሕሊና ውስጥ በአጭሩም በረዥሙም በቀጭኑም በወፍራሙም ብቻ በየትኛውም ሁናቴ ቦታ የለውም ማለት አይቻልም፡፡ ትዝታን በዘፈን፣ትዝታን በግጥም፣ትዝታን በንግግር እንዲሁም ትዝታን በማብሰልሰል ማስታወስ የሕይወታችን መቆዘምያ መንገዶች ናቸው፡፡ አንዳንድ ጊዜ ሰዎች ትዝታዎቻቸውን ሲያወጉ መስማት በራሱ አንዳች ደስታን ይፈጥራል፡፡ በተለይም ዕድሜ ጠገብ የሆኑ አረጋውያን፡፡ በእውነት የተደረጉ ሳይሆኑ በተለያዩ የተረት መጻሕፍት እንደምናነበው ዓይነት ይሆኑብናል፡፡ ግን እውነቶች ናቸው የተኖሩ፡፡ ለምሳሌ “በ25ሳንቲም ክተፎ በላን” ፣ ”በ15 ሳንቲም በአውቶቡስ ደርሶ መልስ እንጓዝ ነበር፡፡ አንድ ጉዞ ብቻ የሚጓዝ ሰው በቀሪው ማስቲካና ከረሜላ  መለወጥ ይችል ነበር” ፣ “1ኪሎ ጤፍ በ20 ሳንቲም ገዝተናል” እነዚህ እውነታዎች ነገር ግን ትዝታዎች ናቸው፡፡ በኢትዮጵያ ሃገራችን የተኖሩ ያልተረሱ ትዝታዎች፡፡ እኔ “ምን ትዝታ አልኝ?” ብዬ ራሴን ብጠይቅ ምንም፡፡ ምክንያቱም አኗኗሬ በጥንቃቄና በፍርሃት በሚኖርበት ጊዜ በመሆኑ፡፡ እድለቢስ ነኝ ልበል?
የሆኖ ሆኖ ዛሬ ለመጻፍ የተነሳሁት በ facebook ገጼ ላይ በተደጋጋሚ ጓደኞቼ post እያደረጉልኝ የተመለከትኩት ፎቶ ግራፍ ነው፡፡ ይህ ፎቶ ግራፍ የሰው ወይም የእንስሳ አልያም የሌላ ሥነ ፍጥረት እነዳይመስላችሁ የደብተር እንጂ፡፡ ደብተሩ ላይ ሁለት ወንድና ሴት ተማሪዎች ቦርሳ አንግተው ከኋላቸው የት/ቤት መለያ የሆነው ሰንደቅ ዓላማ እና የመማርያ ክፍሎች ይታዩበታል፡፡ ታድያ ሁሉም ጓደኞቼ post ሲያደርጉልኝ ተመሳሳይ ጽሑፍ አለው፡፡ ከራስጌው ወይም ከግርጌው “በዚህ ደብተር ተምረው ያውቃሉ?” ይላል፡፡ ነገር ግን እስካሁን like’ን ከመጫን በቀር ምንም ምን ሃሳብ አልሰጠሁበትም፡፡ ለምን? እንጃ ብቻ፡፡ ቁንጥር ብትሆንም ትዝታ አለችኝ፡፡ ከደብተሩ በስተጀርባ፡፡

Monday, July 9, 2012

አሠርቱ ትእዛዛት ፡ክፍል ፫




ሁለተኛው ትእዛዝ

 ‹‹የእግዚአብሔርን የአምላክህን ስም በከንቱ አትጥራ እግዚአብሔር ስሙን በከንቱ የሚጠራውን ከበደል አያነጻውምና።›› ዘጸ 20፡7፡፡ ይህ ትእዛዝ የሚያተኩረው በስመ እግዚአብሔር ላይ ነው፡፡ የአምላካችን የእግዚአብሔር ስም ቅዱስ፣ ታላቅና ድንቅ ነው፡፡ የእግዚአብሔር ስም በልማድ ዝም ብለን የምንጠራው ስም አይደለም፡፡  ‹‹ዘይትህ መልካም መዓዛ አለው ስምህ እንደሚፈስስ ዘይት ነው ስለዚህ ደናግል ወደዱህ።›› መኃ 1፡3 በማለት ጠቢቡ ሰሎሞን እንደታናገረው ስሙን የምንጠራው በጸሎተ እጣን እንደምናደርገው በአክብሮትና በተዋቡ ቃላት ነው፡፡  እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምም ‹‹ብርቱ የሆነ እርሱ በእኔ ታላቅ ሥራ አድርጎአልና፤ ስሙም ቅዱስ ነው።›› ሉቃ 1፡49፡፡ በማለት ነግራናለች፡፡ ልበ አምላክ ዳዊትም በመዝሙሩ ‹‹ስሙ የተቀደሰና የተፈራ ነው›› መዝ 110፡9 ብሎናል፡፡ ጌታችን አምላካችን መድኃኒታችንም ኢየሱስ ክርስቶስ ባስተማረው ጸሎት ‹‹ስምህ ይቀደስ›› ማቴ 6፡9፡፡ በማለት ያስተማረንም የስሙን ቅድስና ልብ እንድል ነው፡፡ ስለዚህ ስሙን ስንጠራ በመፍራትና በመንቀጥቀጥ ለቅዱስ ስሙ አክብሮት በመስጠት መሆን አለበት፡፡ የሰማይ ካህናት ሱራፌል ‹‹ቅዱስ ቅዱስ ቅዱስ የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር ምድር ሁሉ ከክብሩ ተሞልታለች፡፡›› እያሉ ቅዱስ ስሙን ያመሰግናሉ፡፡ ይህም ቅዱስ ስም ሱራፌል በመንቀጥቀጥና በመፍራት የዘመሩለት፣ ቤቱ በጢስ የተሞላበትና የተናወጠበት… ነው፡፡ ኢሳ 6፡1-5፡፡